በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መጽሐፍ ቅዱስን ካጠናሁ የይሖዋ ምሥክር እንድሆን ይጠበቅብኛል?

ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መጽሐፍ ቅዱስን ካጠናሁ የይሖዋ ምሥክር እንድሆን ይጠበቅብኛል?

 በፍጹም። የይሖዋ ምሥክር ያልሆኑ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን ከእኛ ጋር ያጠናሉ። a ዓላማችን ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ምን እንደሚያስተምር እንዲያውቁ መርዳት ነው። ይህን እውቀት ካገኘህ በኋላ ምን እርምጃ እንደምትወስድ መወሰን ያለብህ አንተው ራስህ ነህ። እምነት የግል ጉዳይ እንደሆነ እንገነዘባለን።—ኢያሱ 24:15

በጥናቱ ወቅት የራሴን መጽሐፍ ቅዱስ መጠቀም እችላለሁ?

 አዎ። እርግጥ እኛ በዘመናዊ ቋንቋ የተዘጋጀውን አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ መጠቀም እንመርጣለን፤ አንተም ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም እንዲኖርህ ከፈለግህ በነፃ ልንሰጥህ ፈቃደኞች ነን፤ ሆኖም ከፈለግህ በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቱ ወቅት የራስህን መጽሐፍ ቅዱስ መጠቀም ትችላለህ። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘውን የተስፋና የመዳን መልእክት በየትኛውም የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ውስጥ ማግኘት ትችላለህ።

የእናንተን እምነት ያልተቀበሉ ሰዎችን መጽሐፍ ቅዱስ የምታስጠኑት ለምንድን ነው?

  •   ዋናው ምክንያታችን ለይሖዋ አምላክ ያለን ፍቅር ነው፤ እሱ ክርስቲያኖች የተማሩትን ለሌሎች እንዲያስተምሩ ይፈልጋል። (ማቴዎስ 22:37, 38፤ 28:19, 20) ሰዎች በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን እውነት እንዲማሩ በመርዳት ‘ከአምላክ ጋር አብሮ መሥራት’ ትልቅ ክብር እንደሆነ ይሰማናል።—1 ቆሮንቶስ 3:6-9

  •   ለሰዎች ያለን ፍቅርም እንዲህ እንድናደርግ ያነሳሳናል። (ማቴዎስ 22:39) የተማርናቸውን ግሩም እውነቶች ለሌሎች ማካፈል ደስታ ይሰጠናል።—የሐዋርያት ሥራ 20:35

a የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ፕሮግራማችን ምን ያህል ስፋት እንዳለው መገንዘብ እንድትችል የሚከተለውን አኃዝ ተመልከት፦ በ2023 በየወሩ 7,281,212 የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ፕሮግራሞችን መርተናል፤ በአብዛኞቹ የጥናት ፕሮግራሞች ላይ ከአንድ በላይ ሰዎች ተገኝተዋል። ሆኖም በዚያ ዓመት ተጠምቀው የይሖዋ ምሥክሮች የሆኑት 269,517 ሰዎች ብቻ ናቸው።