ኢሳይያስ 66:1-24

  • እውነተኛና ሐሰተኛ አምልኮ (1-6)

  • ጽዮንና ወንዶች ልጆቿ (7-17)

  • ሰዎች ለአምልኮ በኢየሩሳሌም ይሰበሰባሉ (18-24)

66  ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ሰማይ ዙፋኔ ነው፤ ምድር ደግሞ የእግሬ ማሳረፊያ ናት።+ ታዲያ እናንተ ምን ዓይነት ቤት ልትሠሩልኝ ትችላላችሁ?+ ደግሞስ የማርፍበት ቦታ የት ነው?”+   “እነዚህን ነገሮች ሁሉ የሠራው እጄ ነው፤ሁሉም ወደ ሕልውና የመጡት በዚህ መንገድ ነው” ይላል ይሖዋ።+ “እኔ የማየው ትሑት የሆነውን፣መንፈሱ የተሰበረውንና በቃሌ የሚንቀጠቀጠውን* ሰው ነው።+   በሬን የሚያርድ፣ ሰውን እንደሚገድል ነው።+ በግን የሚሠዋ፣ የውሻን አንገት እንደሚሰብር ነው።+ ስጦታ የሚሰጥ ሰው፣ የአሳማ ደም እንደሚያቀርብ ነው!+ ነጭ ዕጣንን የመታሰቢያ መባ አድርጎ የሚያቀርብ፣+ በአስማታዊ ቃላት እንደሚባርክ* ሰው ነው።+ እነሱ የራሳቸውን መንገድ መርጠዋል፤በአስጸያፊ ነገሮችም ደስ ይሰኛሉ።*   ስለዚህ እነሱን የምቀጣበትን መንገድ እፈልጋለሁ፤+የፈሩትንም ያንኑ ነገር አመጣባቸዋለሁ። ምክንያቱም ስጣራ መልስ የሰጠ ማንም አልነበረም፤ስናገር የሰማ አንድም ሰው አልነበረም።+ በዓይኔ ፊት ክፉ የሆነውን ነገር ማድረጋቸውን ቀጠሉ፤እኔ የማልደሰትበትንም ነገር መረጡ።”+   እናንተ በቃሉ የምትንቀጠቀጡ* ሰዎች ሆይ፣ የይሖዋን ቃል ስሙ፦ “በስሜ የተነሳ የሚጠሏችሁና የሚያገሏችሁ ወንድሞቻችሁ፣ ‘ይሖዋ የተከበረ ይሁን!’ ብለዋል።+ ሆኖም አምላክ ይገለጣል፤ ደስታንም ያጎናጽፋችኋል፤እነሱም ለኀፍረት ይዳረጋሉ።”+   ከከተማዋ ሁካታ፣ ከቤተ መቅደሱም ድምፅ ይሰማል! ይህም ይሖዋ ለጠላቶቹ የሚገባቸውን ብድራት በሚከፍላቸው ጊዜ የሚሰማ ድምፅ ነው።   እሷ ገና ምጥ ሳይጀምራት ወለደች።+ ምጥ ሳይዛት በፊት ወንድ ልጅ ተገላገለች።   እንዲህ ያለ ነገር ማን ሰምቶ ያውቃል? እንዲህ ያሉ ነገሮችስ ማን አይቶ ያውቃል? አገር በአንድ ቀን ይወለዳል? ወይስ ብሔር በአንድ ጊዜ ይወለዳል? ሆኖም ጽዮን እንዳማጠች ወዲያው ወንዶች ልጆቿን ወልዳለች።   “ማህፀኑን ከከፈትኩ በኋላ ልጁ እንዳይወለድ አደርጋለሁ?” ይላል ይሖዋ። “ወይስ ምጡ እንዲፋፋም ካደረግኩ በኋላ ማህፀኑን እዘጋለሁ?” ይላል አምላክሽ። 10  እናንተ የምትወዷት ሁሉ፣+ ከኢየሩሳሌም ጋር ሐሴት አድርጉ፤ ከእሷም ጋር ደስ ይበላችሁ።+ ለእሷ የምታዝኑ ሁሉ ከእሷ ጋር እጅግ ደስ ይበላችሁ፤ 11  የሚያጽናኑ ጡቶቿን ትጠባላችሁና፤ ሙሉ በሙሉም ትረካላችሁ፤እስኪበቃችሁም ድረስ ትጠጣላችሁ፤ በክብሯም ብዛት ሐሴት ታደርጋላችሁ። 12  ይሖዋ እንዲህ ይላልና፦ “እነሆ፣ ሰላምን እንደ ወንዝ፣+የብሔራትንም ክብር እንደሚያጥለቀልቅ ጅረት አፈስላታለሁ።+ እናንተም ትጠባላችሁ፤ ጀርባዋም ላይ ታዝላችኋለች፣ጭኗም ላይ ሆናችሁ ትዘላላችሁ። 13  እናት ልጇን እንደምታጽናና፣እኔም እናንተን ሁልጊዜ አጽናናችኋለሁ፤+በኢየሩሳሌምም ትጽናናላችሁ።+ 14  እናንተ ይህን ታያላችሁ፤ ልባችሁም ሐሴት ያደርጋል፤አጥንቶቻችሁ እንደ ሣር ይለመልማሉ። የይሖዋም እጅ* በአገልጋዮቹ ዘንድ ትታወቃለች፤ጠላቶቹን ግን ያወግዛቸዋል።”+ 15  “ይሖዋ፣ ብድራቱን በታላቅ ቁጣ ለመመለስ፣በእሳት ነበልባልም ለመገሠጽ+እንደ እሳት ሆኖ ይመጣልና፤+ሠረገሎቹም እንደ አውሎ ነፋስ ይመጣሉ።+ 16  ይሖዋ በእሳት ፍርዱን ይፈጽማልና፤አዎ፣ በሥጋ ለባሽ* ሁሉ ላይ በሰይፍ ፍርዱን ይፈጽማል፤በይሖዋ እጅ የሚገደሉትም ብዙ ይሆናሉ። 17  ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “መሃል ላይ ያለውን ተከትለው ወደ አትክልት ቦታዎቹ*+ ለመግባት ሲሉ ራሳቸውን የሚቀድሱና የሚያነጹ፣ የአሳማ ሥጋና አስጸያፊ ነገር እንዲሁም አይጥ የሚበሉ ሁሉ+ በአንድነት ይጠፋሉ። 18  እኔ ሥራቸውንና ሐሳባቸውን ስለማውቅ፣ ከሁሉም ብሔራትና ቋንቋዎች የተውጣጡ ሰዎችን ለመሰብሰብ እመጣለሁ፤ እነሱም መጥተው ክብሬን ያያሉ።” 19  “በመካከላቸው ምልክት አቆማለሁ፤ ከተረፉት መካከል አንዳንዶቹን ወደ ብሔራት ይኸውም ወደ ተርሴስ፣+ ወደ ፑል እና ወደ ሉድ+ እልካለሁ። በቱባልና በያዋን+ ወዳሉት ቀስተኞች እልካቸዋለሁ። ስለ እኔ ወዳልሰሙ ወይም ክብሬን ወዳላዩ፣ ርቀው በሚገኙ ደሴቶች ውስጥ ወደሚኖሩ ሕዝቦችም እልካቸዋለሁ፤ እነሱም በብሔራት መካከል ክብሬን ያውጃሉ።+ 20  የእስራኤል ልጆች በንጹሕ ዕቃ ስጦታ ይዘው ወደ ይሖዋ ቤት እንደሚያመጡ፣ ወንድሞቻችሁን ሁሉ ለይሖዋ ስጦታ እንዲሆኑ ከየብሔራቱ በፈረሶች፣ በሠረገሎች፣ ጥላ ባላቸው ጋሪዎች፣ በበቅሎዎችና በፈጣን ግመሎች ጭነው ወደተቀደሰው ተራራዬ ወደ ኢየሩሳሌም ያመጧቸዋል”+ ይላል ይሖዋ። 21  “በተጨማሪም አንዳንዶቹን ካህናት፣ ሌሎቹን ደግሞ ሌዋውያን እንዲሆኑ እወስዳለሁ” ይላል ይሖዋ። 22  “እኔ የምሠራቸው አዲስ ሰማያትና አዲስ ምድር+ በፊቴ ጸንተው እንደሚኖሩ ሁሉ የእናንተም ዘርና ስማችሁ እንዲሁ ጸንቶ ይኖራል”+ ይላል ይሖዋ። 23  “ከአንዱ ወር መባቻ እስከ ሌላው ወር መባቻ እንዲሁም ከአንዱ ሰንበት እስከ ሌላው ሰንበት፣ሰው* ሁሉ በፊቴ ለመስገድ* ይመጣል”+ ይላል ይሖዋ። 24  “እነሱም ሄደው በእኔ ላይ ያመፁትን ሰዎች ሬሳ ያያሉ፤በእነሱ ላይ ያሉት ትሎች አይሞቱምና፤እሳታቸውም አይጠፋም፤+ለሰዎችም* ሁሉ አስጸያፊ ነገር ይሆናሉ።”

የግርጌ ማስታወሻዎች

ወይም “ስለ ቃሌ የሚጨነቀውን።”
ወይም “ነፍሳቸውም በአስጸያፊ ነገሮች ደስ ትሰኛለች።”
“ጣዖት እንደሚያወድስ” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “ስለ ቃሉ የምትጨነቁ።”
ወይም “ኃይል።”
ወይም “በሰዎች።”
ጣዖት አምልኮ የሚካሄድባቸውን ልዩ የሆኑ የአትክልት ቦታዎች ያመለክታል።
ቃል በቃል “ሥጋ።”
ወይም “ለማምለክ።”
ቃል በቃል “ለሥጋም።”