ዘፍጥረት 2:1-25

  • በሰባተኛው ቀን አምላክ ከሥራው አረፈ (1-3)

  • የሰማይና የምድር ፈጣሪ የሆነው ይሖዋ አምላክ (4)

  • የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት በኤደን ገነት (5-25)

    • ሰው ከአፈር ተሠራ (7)

    • የተከለከለው የእውቀት ዛፍ (15-17)

    • ሴት ከአዳም ተፈጠረች (18-25)

2  በዚህ መንገድ ሰማያትንና ምድርን እንዲሁም በውስጣቸው ያለውን ነገር ሁሉ* የመፍጠሩ ሥራ ተጠናቀቀ።+  በሰባተኛውም ቀን አምላክ ይሠራው የነበረውን ሥራ አጠናቀቀ፤ በሰባተኛውም ቀን ይሠራው ከነበረው ሥራ ሁሉ ማረፍ ጀመረ።+  አምላክም ሰባተኛውን ቀን ባረከው እንዲሁም ቀደሰው፤ ምክንያቱም አምላክ ከመፍጠር ሥራው ሁሉ፣ ሊሠራ ካሰበው ነገር ሁሉ ያረፈው ከዚያ ቀን አንስቶ ነው።  ሰማያትና ምድር በተፈጠሩበት ጊዜ፣ ይሖዋ* አምላክ ምድርንና ሰማይን በሠራበት+ ቀን የተከናወነው ነገር ይህ ነው።  በዚህ ጊዜ በምድር ላይ ምንም ዓይነት የሜዳ ቁጥቋጦ አልነበረም፤ እንዲሁም በሜዳ ላይ ምንም ዓይነት ተክል አልበቀለም፤ ምክንያቱም ይሖዋ አምላክ በምድር ላይ ዝናብ እንዲዘንብ አላደረገም ነበር፤ መሬቱን የሚያለማም ሰው አልነበረም።  ይሁንና ተን ከምድር እየተነሳ መላውን መሬት ያጠጣ ነበር።  ይሖዋ አምላክም ሰውን ከምድር አፈር ሠራው፤+ በአፍንጫውም የሕይወትን እስትንፋስ እፍ አለበት፤+ ሰውየውም ሕያው ሰው* ሆነ።+  በተጨማሪም ይሖዋ አምላክ በስተ ምሥራቅ፣ በኤደን የአትክልት ስፍራ ተከለ፤+ የሠራውንም ሰው+ በዚያ አስቀመጠው።  ከዚያም ይሖዋ አምላክ ለማየት የሚያስደስተውንና ለምግብነት መልካም የሆነውን ዛፍ ሁሉ ከመሬት አበቀለ። በተጨማሪም በአትክልቱ ስፍራ መካከል የሕይወት ዛፍ+ እንዲሁም የመልካምና ክፉ እውቀት ዛፍ+ አበቀለ። 10  የአትክልቱን ስፍራ የሚያጠጣ ወንዝ ከኤደን ወጥቶ ይፈስ ነበር፤ ከዚያም ተከፋፍሎ አራት ወንዝ* ሆነ። 11  የመጀመሪያው ወንዝ ስም ፊሶን ነው፤ ይህ ወንዝ ወርቅ የሚገኝበትን መላውን የሃዊላ ምድር የሚከብ ነው። 12  የዚያ አገር ወርቅ ምርጥ ነው። በተጨማሪም በዚያ ጥሩ መዓዛ ያለው ሙጫና* የኦኒክስ ድንጋዮች ይገኛሉ። 13  የሁለተኛው ወንዝ ስም ግዮን ነው፤ ይህ ወንዝ መላውን የኢትዮጵያ* ምድር የሚከብ ነው። 14  የሦስተኛው ወንዝ ስም ጤግሮስ*+ ነው፤ ይህ ወንዝ ከአሦር+ በስተ ምሥራቅ የሚፈስ ነው። አራተኛው ወንዝ ደግሞ ኤፍራጥስ+ ነው። 15  ይሖዋ አምላክ ሰውየውን ወስዶ እንዲያለማውና እንዲንከባከበው በኤደን የአትክልት ስፍራ አስቀመጠው።+ 16  በተጨማሪም ይሖዋ አምላክ ለሰውየው ይህን ትእዛዝ ሰጠው፦ “በአትክልቱ ስፍራ ውስጥ ከሚገኘው ዛፍ ሁሉ እስክትረካ ድረስ መብላት ትችላለህ።+ 17  ከመልካምና ክፉ እውቀት ዛፍ ግን አትብላ፤ ምክንያቱም ከዚህ ዛፍ በበላህ ቀን በእርግጥ ትሞታለህ።”+ 18  ከዚያም ይሖዋ አምላክ “ሰውየው ብቻውን መሆኑ መልካም አይደለም። ማሟያ የምትሆነውን ረዳት እሠራለታለሁ”+ አለ። 19  ይሖዋ አምላክም እያንዳንዱን የዱር እንስሳ እንዲሁም በሰማያት ላይ የሚበረውን እያንዳንዱን ፍጥረት ከአፈር ሠርቶ ነበር፤ ከዚያም ሰውየው እያንዳንዳቸውን ምን ብሎ እንደሚጠራቸው ለማየት ሁሉንም ወደ እሱ አመጣቸው፤ ሰውየው ለእያንዳንዱ ሕያው ፍጡር* የሰጠው መጠሪያም የዚያ ፍጡር ስም ሆነ።+ 20  በመሆኑም ሰውየው ለቤት እንስሳት በሙሉ፣ በሰማያት ላይ ለሚበርሩ ፍጥረታት እንዲሁም ለዱር እንስሳት ሁሉ ስም አወጣላቸው፤ ለሰው ግን ማሟያ የሚሆን ረዳት አልነበረውም። 21  ስለሆነም ይሖዋ አምላክ በሰውየው ላይ ከባድ እንቅልፍ ጣለበት፤ እንቅልፍ ወስዶት ሳለም ከጎድን አጥንቶቹ አንዷን ወሰደ፤ ቦታውንም በሥጋ ደፈነው። 22  ይሖዋ አምላክም ከሰውየው የወሰዳትን የጎድን አጥንት ሴት አድርጎ ሠራት፤ ሴቲቱንም ወደ ሰውየው አመጣት።+ 23  በዚህ ጊዜ ሰውየው እንዲህ አለ፦ “እንግዲህ እሷ የአጥንቶቼ አጥንት፣የሥጋዬም ሥጋ ናት። እሷ ከወንድ ስለተገኘች+‘ሴት’ ትባላለች።” 24  በዚህም ምክንያት ሰው ከአባቱና ከእናቱ ይለያል፤ ከሚስቱም ጋር ይጣበቃል።* ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ።+ 25  ሰውየውም ሆነ ሚስቱ ራቁታቸውን ነበሩ፤+ እንደዚያም ሆኖ ኀፍረት አይሰማቸውም ነበር።

የግርጌ ማስታወሻዎች

ቃል በቃል “ሠራዊታቸውን ሁሉ።”
አምላክ ብቻ የሚጠራበት የግል ስሙ ይኸውም יהוה (የሐወሐ) ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀሰው እዚህ ላይ ነው። ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ4ን ተመልከት።
ወይም “ነፍስ።” በዕብራይስጥ ነፈሽ ሲሆን ቃል በቃል ሲተረጎም “የሚተነፍስ ፍጥረት” ማለት ነው። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።
ቃል በቃል “አራት ራስ።”
ይህ ሙጫ በሞቃታማ አካባቢዎች ከሚበቅሉ ትናንሽ ዛፎች የሚገኝ ከርቤ የሚመስል ጥሩ መዓዛ ያለው ሙጫ ነው።
ወይም “የኩሽ።” ይህ ቦታ ከየት እስከ የት ያለውን አካባቢ እንደሚያመለክት በትክክል አይታወቅም።
ወይም “ሂዲኬል።”
ወይም “ነፍስ።”
ወይም “አብሮ ይኖራል።”