በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

’ማስተዋልሽ የተባረከ ይሁን!’

’ማስተዋልሽ የተባረከ ይሁን!’

እነዚህ ቃላት በጥንቷ እስራኤል ይኖር የነበረው ዳዊት አንዲትን ሴት ለማመስገን የተናገራቸው ቃላት ናቸው። ይህች ሴት አቢጋኤል ትባላለች። ዳዊት አቢጋኤልን ያመሰገናት ለምንድን ነው? እኛስ ከእሷ ምን እንማራለን?

ዳዊት ይህችን ባለትዳር ሴት ያገኛት ከንጉሥ ሳኦል ሸሽቶ በዱር በነበረበት ወቅት ነው። አቢጋኤል በደቡባዊ ይሁዳ ተራራማ አካባቢ የሚኖር፣ ብዙ በጎችና ፍየሎች የነበሩት ናባል የተባለ ሀብታም ሰው ሚስት ነበረች። ዳዊትና ሰዎቹ ለናባል መንጎችና እረኞች “እንደ መከላከያ ቅጥር” ሆነውላቸው ነበር። ከጊዜ በኋላ ዳዊት፣ ናባል ‘የቻለውን ያህል’ ምግብ እንዲሰጠው ለመጠየቅ መልእክተኞችን ላከ። (1 ሳሙ. 25:8, 15, 16) ዳዊትና ሰዎቹ የናባልን ንብረት ለመጠበቅ ካደረጉት ነገር አንጻር ሲታይ ዳዊት የጠየቀው ነገር ከባድ አልነበረም።

ናባል የሚለው ስም “የማያመዛዝን” ወይም “ጅል” የሚል ትርጉም ያለው ሲሆን ናባልም ልክ እንደ ስሙ ነበር። የዳዊትን ጥያቄ ከመቀበል ይልቅ በስድብና በኃይለ ቃል ምላሽ ሰጠ። ናባል እንዲህ ያለ መጥፎ ምላሽ በመስጠቱ ዳዊት እሱን ለመቅጣት ተዘጋጀ። ናባል በፈጸመው የሞኝነት ድርጊት የተነሳ እሱም ሆነ ቤተሰቡ ለጥፋት ሊዳረጉ ሆነ።—1 ሳሙ. 25:2-13, 21, 22

አቢጋኤል፣ ዳዊት ሊያደርግ ያሰበው ነገር የሚያስከትለውን አስከፊ ውጤት በመገንዘቧ በድፍረት ጣልቃ ገብታ እርምጃ ወሰደች። ዳዊት ከይሖዋ ጋር ያለውን ዝምድና በማሰብ ሊወስድ ያሰበውን እርምጃ እንዲተው በአክብሮት ለመነችው። በተጨማሪም ንጉሥ እንዲሆን ለተቀባው ለዳዊትና ለሰዎቹ በቂ ምግብ አዘጋጅታ ሰጠቻቸው። ዳዊትም በምላሹ ይሖዋ በእሷ በመጠቀም በአምላክ ፊት በደለኛ እንዲሆን ሊያደርገው የሚችለውን ነገር ከማድረግ እንዲቆጠብ እንደረዳው ተናገረ። ከዚያም ዳዊት አቢጋኤልን “[ማስተዋልሽ] የተባረከ ይሁን! በዚህ ዕለት በራሴ ላይ የደም ዕዳ እንዳላመጣ . . . ስለጠበቅሽኝ አንቺም የተባረክሽ ሁኚ” አላት።—1 ሳሙ. 25:18, 19, 23-35

ለተደረገልን መልካም ነገር አድናቆት የለሽ በመሆን ናባልን መምሰል እንደማንፈልግ የታወቀ ነው። በተጨማሪም አንድ መጥፎ ነገር ሊፈጸም እንደሆነ ከተገነዘብን ይህ ነገር እንዳይፈጸም የቻልነውን ሁሉ ማድረጋችን አስፈላጊ ነው። እኛም “ማስተዋልንና እውቀትን አስተምረኝ” በማለት ለአምላክ የተናገረውን መዝሙራዊ ስሜት እናስተጋባለን።—መዝ. 119:66

እንዲህ ካደረግን ሌሎች ሰዎች ድርጊታችን ጥበብ ወይም ማስተዋል የሚንጸባረቅበት እንደሆነ ሊመለከቱ ይችላሉ። እነዚህ ሰዎች አፋቸውን አውጥተው ባይናገሩትም እንኳ ‘ማስተዋልሽ የተባረከ ይሁን!’ እንዳለው እንደ ዳዊት ዓይነት ስሜት ሊሰማቸው ይችላል።