በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መንፈሳዊነት

መንፈሳዊነት

በመጀመሪያው ርዕስ ላይ እንደተገለጸው ብዙዎች መጽሐፍ ቅዱስ የአምላክ ቃል እንደሆነ ያምናሉ። መጽሐፍ ቅዱስን ሲያነቡና ምክሩን ተግባራዊ ሲያደርጉ መንፈሳዊነታቸው ያድጋል፤ የሕይወትን ዓላማም ይገነዘባሉ።

መጽሐፍ ቅዱስ ‘መንፈሳዊነት’ የሚለውን ቃል የሚጠቀመው የሰዎችን የሕይወት ጎዳና ወይም አኗኗር ለማመልከት ነው። (ይሁዳ 18, 19) ሥጋዊ አስተሳሰብ ያለው ሰው ሕይወቱ የሚያጠነጥነው በራሱ ዙሪያ ነው፤ መንፈሳዊ ሰው ግን ሕይወቱን የሚመራው አምላክ ባወጣቸው መሥፈርቶች መሠረት ነው።—ኤፌሶን 5:1

ተስፋ

የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ “በችግር ጊዜ ተስፋ የምትቆርጥ ከሆነ ጉልበትህ እጅግ ይዳከማል።”—ምሳሌ 24:10 የግርጌ ማስታወሻ

ምን ማለት ነው? ተስፋ ከቆረጥን የሕይወትን ውጣ ውረድ ለመወጣት የሚያስችል አቅም እናጣለን። ተስፋ ካለን ግን ችግሮችን ለመቋቋም የሚያስችል ድፍረት ይኖረናል። የሚያጋጥሙን ችግሮች ጊዜያዊ እንደሆኑ ማወቃችን ያጽናናናል፤ እንዲያውም አንዳንድ ጊዜ ችግሮቹ የኋላ ኋላ መልካም ውጤት ሊያስገኙልን ይችላሉ።

ምን ማድረግ ትችላለህ? ስለ ወደፊቱ ጊዜ አዎንታዊ አመለካከት ለማዳበር ጥረት አድርግ። ወደፊት ሊያጋጥም ስለሚችለው ነገር ከመጨነቅ ወይም ሁኔታዎች በራሳቸው እስኪመቻቹ ድረስ ከመጠበቅ ይልቅ ካወጣኸው ግብ ጋር የሚስማማ እርምጃ ውሰድ። እርግጥ “ያልተጠበቁ ክስተቶች” ሊያጋጥሙ ይችላሉ። (መክብብ 9:11) ሆኖም አብዛኛውን ጊዜ ነገሮች ያሰብነውን ያህል መጥፎ አይሆኑም። በመሆኑም መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ የሚል ምክር ይሰጣል፦ “በማለዳ ዘርህን ዝራ፤ እስከ ምሽትም ድረስ እጅህ ሥራ አይፍታ፤ ይህ ወይም ያ የትኛው እንደሚያድግ ወይም ደግሞ ሁለቱም ይጸድቁ እንደሆነ አታውቅምና።”—መክብብ 11:6

በአእምሯችን ለሚጉላሉ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት

የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ “ማስተዋል ስጠኝ። . . . የቃልህ ፍሬ ነገር እውነት ነው።”—መዝሙር 119:144, 160

ምን ማለት ነው? መጽሐፍ ቅዱስ በሁሉም ሰው አእምሮ ውስጥ ለሚጉላሉ ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል። ለምሳሌ የሚከተሉትን ጥያቄዎች መልስ ይዟል፦

  • የመጣነው ከየት ነው?

  • የተፈጠርነው ለምንድን ነው?

  • ስንሞት ምን እንሆናለን?

  • ሕይወት በቃ ይኸው ነው?

በዓለም ዙሪያ የሚኖሩ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ለእነዚህና ለሌሎችም ጥያቄዎች የሚሰጠውን መልስ በመመርመራቸው የተሻለ ሕይወት መምራት ችለዋል።

ምን ማድረግ ትችላለህ? መጽሐፍ ቅዱስ ምን እንደሚያስተምር መርምር። መጽሐፍ ቅዱስን እንዲያስተምሩህ የይሖዋ ምሥክሮችን መጠየቅ ትችላለህ። ወይም ደግሞ jw.org የተባለውን ድረ ገጻችንን መጎብኘት አሊያም በስብሰባዎቻችን ላይ መገኘት ትችላለህ፤ ስብሰባዎቻችን ለሕዝብ ክፍት ናቸው፤ እንዲሁም መግቢያ በነፃ ነው።

ሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያዎች

መጽሐፍ ቅዱስን መማር የሚኖርብን ለምንድን ነው? የተባለውን ቪዲዮ ተመልከት። ቪዲዮው jw.org ላይ ከ880 በሚበልጡ ቋንቋዎች ይገኛል።

ለመንፈሳዊ ፍላጎትህ ትኩረት ስጥ።

“መንፈሳዊ ነገሮችን የተጠሙ ደስተኞች ናቸው።”​—ማቴዎስ 5:3

ስለ እውነተኛው አምላክ ተማር።

‘አምላክ ሰዎች እንዲፈልጉትና አጥብቀው በመሻት እንዲያገኙት ይፈልጋል፤ እሱ ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም።’​—የሐዋርያት ሥራ 17:27

መጽሐፍ ቅዱስን አንብብ፤ እንዲሁም ባነበብከው ላይ አሰላስል።

“በይሖዋ * ሕግ ደስ ይለዋል፤ ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያሰላስለዋል። . . . የሚሠራውም ሁሉ ይሳካለታል።”​—መዝሙር 1:2, 3 የግርጌ ማስታወሻ

^ አን.23 መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው የአምላክ የግል ስም ይሖዋ ነው።