በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አሳ፣ ኢዮሳፍጥ፣ ሕዝቅያስ፣ ኢዮስያስ

ይሖዋን በሙሉ ልብ አገልግሉ!

ይሖዋን በሙሉ ልብ አገልግሉ!

“እባክህ ይሖዋ ሆይ፣ በታማኝነትና በሙሉ ልብ በፊትህ እንዴት እንደተመላለስኩ [አስታውስ]።”—2 ነገ. 20:3

መዝሙሮች፦ 36, 54

1-3. ይሖዋን “በሙሉ ልብ” ማገልገል ሲባል ምን ማለት ነው? ምሳሌ ስጥ።

ፍጽምና የጎደለን በመሆናችን ብዙ ጊዜ ስህተት እንሠራለን። ደስ የሚለው ነገር ግን፣ ንስሐ እስከገባንና በኢየሱስ ቤዛዊ መሥዋዕት በማመን በትሕትና ምሕረት እስከጠየቅን ድረስ ይሖዋ ‘እንደ ኃጢአታችን አያደርግብንም።’ (መዝ. 103:10) ያም ቢሆን ዳዊት ለሰለሞን እንደነገረው በየዕለቱ ለይሖዋ የምናቀርበው አምልኮ ተቀባይነት እንዲያገኝ እሱን ‘በሙሉ ልብ ማገልገል’ ይኖርብናል። (1 ዜና 28:9) ታዲያ ፍጽምና የጎደለን ሰዎች ሆነን እያለን እንዲህ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

2 የንጉሥ አሳን እና የንጉሥ አሜስያስን ሕይወት ማወዳደራችን ለዚህ ጥያቄ መልስ ለማግኘት ይረዳናል። ሁለቱም የይሁዳ ነገሥታት በይሖዋ ፊት ትክክል የሆነውን አድርገዋል፤ ይሁንና አሳ ይህን ያደረገው በሙሉ ልቡ ነበር። (2 ዜና 15:16, 17፤ 25:1, 2፤ ምሳሌ 17:3) ሁለቱም ነገሥታት ፍጽምና የጎደላቸው ከመሆናቸውም ሌላ የተለያዩ ስህተቶችን ሠርተዋል። ሆኖም አሳ ‘ሙሉ በሙሉ ለአምላክ ያደረ’ ስለነበር በጥቅሉ ሲታይ ከአምላክ ጎዳና ፈቀቅ አላለም። (1 ዜና 28:9 ግርጌ) በሌላ በኩል ግን አሜስያስ ለይሖዋ ሙሉ በሙሉ ያደረ ሰው አልነበረም። የአምላክን ጠላቶች ድል ካደረገ በኋላ የእነሱን አማልክት ይዞ በመምጣት ያመልካቸው ጀመር።—2 ዜና 25:11-16

3 አምላክን “በሙሉ ልብ” ማገልገል ሲባል ምንጊዜም ለእሱ ሙሉ በሙሉ ያደሩ መሆንን ያካትታል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “ልብ” የሚለው ቃል ብዙውን ጊዜ የሚያመለክተው የአንድን ሰው ውስጣዊ ማንነት ነው። ይህም ምኞቱን፣ አስተሳሰቡን፣ ዝንባሌውን፣ አመለካከቱን፣ ችሎታውን፣ ግቦቹንና አንድን ነገር ለማድረግ የሚገፋፋውን ስሜት ያጠቃልላል። በመሆኑም ይሖዋን በሙሉ ልቡ የሚያገለግል ሰው ግብዝ አይደለም። ይሖዋን የሚያመልከው ለይስሙላ አይደለም። እኛም ፍጽምና የጎደለን ሰዎች ብንሆንም እንኳ ከግብዝነት በመራቅ ምንጊዜም ለአምላክ ሙሉ በሙሉ ያደርን ከሆንን በሙሉ ልባችን ልናገለግለው እንችላለን።—2 ዜና 19:9

4. በዚህ ርዕስ ላይ ምን እንመረምራለን?

4 አምላክን በሙሉ ልብ ማገልገል ሲባል ምን ማለት እንደሆነ ለመረዳት የአሳን እንዲሁም በሙሉ ልባቸው ለአምላክ ያደሩ ሦስት የይሁዳ ነገሥታትን ሕይወት እንመርምር። እነዚህ ነገሥታት ኢዮሳፍጥ፣ ሕዝቅያስና ኢዮስያስ ናቸው። አራቱም ነገሥታት ስህተት የሠሩ ቢሆንም ይሖዋ እንደተደሰተባቸው ተገልጿል። አምላክ በሙሉ ልባቸው እንዳገለገሉት የተሰማው ለምንድን ነው? እኛስ የእነሱን ምሳሌ መከተል የምንችለው እንዴት ነው?

የአሳ ልብ “በይሖዋ ዘንድ ሙሉ ነበር”

5. አሳ ምን ቆራጥ እርምጃ ወስዷል?

5 አሳ፣ የእስራኤል ብሔር ለሁለት ከተከፈለ በኋላ በይሁዳ መንግሥት ላይ ከነገሡት ነገሥታት ሦስተኛው ነው። አሳ ግዛቱን ከጣዖት አምልኮ ያጸዳ ሲሆን የቤተ መቅደስ ቀላጮችን ከምድሪቱ አባርሯል። አያቱን ማአካን እንኳ “ጸያፍ ጣዖት ሠርታ ስለነበር ከእመቤትነቷ [ሽሯታል]።” (1 ነገ. 15:11-13) በተጨማሪም የይሁዳ ሰዎች “ይሖዋን እንዲፈልጉ እንዲሁም ሕጉንና ትእዛዙን እንዲያከብሩ” አበረታቷቸዋል። በእርግጥም አሳ እውነተኛው አምልኮ እንዲስፋፋ ጥረት አድርጓል።—2 ዜና 14:4

6. ኢትዮጵያውያን ምድሪቱን በወረሩበት ወቅት አሳ ምን አደረገ?

6 ይሖዋ፣ አሳ ከነገሠ በኋላ በነበሩት አሥር ዓመታት በይሁዳ ግዛት ውስጥ ሰላም እንዲሰፍን አድርጓል። ከዚያ በኋላ ግን ኢትዮጵያዊው ዛራ 1,000,000 ሰዎችንና 300 ሠረገሎችን ያቀፈ ሠራዊት አስከትሎ በይሁዳ መንግሥት ላይ ዘመተ። (2 ዜና 14:1, 6, 9, 10) አሳ እንዲህ ዓይነት አስቸጋሪ ሁኔታ ሲያጋጥመው ምን አደረገ? ወደ ይሖዋ በመጸለይ በእሱ ሙሉ በሙሉ እንደሚተማመን አሳይቷል። (2 ዜና መዋዕል 14:11ን አንብብ።) አምላክም አሳ ላቀረበው ከልብ የመነጨ ጸሎት ምላሽ ሰጥቶታል፤ የኢትዮጵያውያንን ሠራዊት በማጥፋት ታላቅ ድል እንዲቀዳጅ ረድቶታል። (2 ዜና 14:12, 13) ይሖዋ፣ ታማኝ ያልሆኑ ነገሥታት እንኳ በጠላቶቻቸው ላይ ድል እንዲቀዳጁ ያደረገባቸው ጊዜያት አሉ፤ እነዚህን ነገሥታት የረዳቸው ለስሙ ሲል ነው። (1 ነገ. 20:13, 26-30) ይሖዋ፣ አሳ ላቀረበው ጸሎት መልስ የሰጠው ግን ይህ ንጉሥ በእሱ ስለታመነ ነው። እርግጥ ነው፣ ከጊዜ በኋላ አሳ ከባድ ስህተት ሠርቷል። በአንድ ወቅት እርዳታ ሲያስፈልገው ይሖዋን ከመጠየቅ ይልቅ ወደ ሶርያ ንጉሥ መልእክተኞች ልኳል። (1 ነገ. 15:16-22) ያም ሆኖ አምላክ ለአሳ የነበረውን አመለካከት መጽሐፍ ቅዱስ ሲገልጽ “አሳ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ልቡ በይሖዋ ዘንድ ሙሉ ነበር” ይላል። እኛስ መልካም የሆነውን በማድረግ ረገድ የአሳን ምሳሌ መከተል የምንችለው እንዴት ነው?—1 ነገ. 15:14

7, 8. የአሳን ምሳሌ መከተል የምትችለው በየትኞቹ መንገዶች ነው?

7 እያንዳንዳችን ሙሉ ለሙሉ ለአምላክ ያደርን መሆናችንን ለማወቅ ልባችንን መመርመር ይኖርብናል። ራሳችንን እንዲህ ብለን መጠየቅ እንችላለን፦ ‘ይሖዋን ለማስደሰት፣ ከእውነተኛው አምልኮ ጎን ለመቆም እንዲሁም የጉባኤውን ንጽሕና ለመጠበቅ ቁርጥ ውሳኔ አድርጌያለሁ?’ አሳ፣ አያቱን ማአካን እንደ ንጉሡ እናት ተቆጥራ ከተሰጣት ቦታ ለመሻር ምን ያህል ድፍረት ጠይቆበት እንደሚሆን መገመት እንችላለን። እርግጥ ነው፣ አንተ የምታውቃቸው ሰዎች እንደ ማአካ ዓይነት ድርጊት አይፈጽሙ ይሆናል፤ ይሁንና አሳ ያሳየውን ዓይነት ቅንዓት ማሳየት አስፈላጊ የሚሆንበት ሁኔታ ሊያጋጥምህ ይችላል። ለምሳሌ ያህል፣ አንድ የቤተሰብህ አባል ወይም የቅርብ ጓደኛህ ኃጢአት ቢፈጽምና ንስሐ ሳይገባ ቀርቶ ቢወገድ ምን ታደርጋለህ? ከዚህ ግለሰብ ጋር ያለህን ግንኙነት በማቋረጥ ቁርጥ ያለ እርምጃ ትወስዳለህ? በዚህ ጊዜ ልብህ ምን እንድታደርግ ይገፋፋሃል?

8 አንዳንድ ጊዜ አንተም እንደ አሳ፣ ልትቋቋመው የማትችለው ዓይነት ፈተና እንደገጠመህ ሆኖ ይሰማህ ይሆናል፤ በዚህ ጊዜ አሳ እንዳደረገው ሁሉ አንተም በአምላክ ላይ በመታመን እሱን በሙሉ ልብህ እንደምታገለግለው ማሳየት ትችላለህ። ለምሳሌ አብረውህ የሚማሩት ልጆች ወይም አስተማሪዎችህ የይሖዋ ምሥክር በመሆንህ ያሾፉብህና ይቀልዱብህ ይሆናል። አሊያም ደግሞ የሥራ ባልደረቦችህ በመንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ለመካፈል ስትል እረፍት በመውሰድህ ወይም አዘውትረህ ተጨማሪ ሰዓት ባለመሥራትህ እንደ ሞኝ ሊቆጥሩህ ይችላሉ። እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ሲያጋጥምህ አሳ እንዳደረገው ወደ አምላክ ጸልይ። በይሖዋ በመታመን፣ ትክክል የሆነውን ነገር በድፍረት ማድረግህን ቀጥል። አምላክ አሳን እንዳበረታውና እንደረዳው ሁሉ አንተንም እንደሚያበረታህ አስታውስ።

9. ከስብከቱ ሥራ ጋር በተያያዘ ይሖዋን በሙሉ ልብ እንደምናገለግል ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

9 የአምላክ አገልጋዮች ከራሳቸውም አልፈው ስለ ሌሎች ያስባሉ። አሳ፣ ሌሎችም እውነተኛውን አምልኮ እንዲከተሉ አበረታቷል። እኛም በተመሳሳይ ሌሎች “ይሖዋን እንዲፈልጉ” እንረዳለን። ለአምላክ ባለን ልባዊ ፍቅርና ሰዎች የዘላለም ሕይወት እንዲያገኙ ባለን ልባዊ ፍላጎት ተነሳስተን ለጎረቤቶቻችንና ለሌሎች ሰዎች ስንመሠክር ይሖዋ ምን ያህል ይደሰት ይሆን!

ኢዮሳፍጥ ይሖዋን ፈልጓል

10, 11. የኢዮሳፍጥን ምሳሌ መከተል የምንችለው እንዴት ነው?

10 የአሳ ልጅ የሆነው ኢዮሳፍጥ “በአባቱ በአሳ መንገድ [ሄዷል]።” (2 ዜና 20:31, 32) ይህን ያደረገው እንዴት ነው? እንደ አባቱ ሁሉ ኢዮሳፍጥም ሕዝቡ ይሖዋን እንዲፈልግ አበረታቷል። “የይሖዋን ሕግ መጽሐፍ” የሚያስተምሩ ሰዎችን ወደ ይሁዳ ከተሞች ልኳል። (2 ዜና 17:7-10) ከዚህም በላይ ሰሜናዊው የእስራኤል መንግሥት በሚያስተዳድረው ክልል ይኸውም በተራራማው የኤፍሬም ምድር የሚኖረውን ሕዝብ እንኳ ‘ወደ ይሖዋ ለመመለስ’ እዚያ ድረስ ሄዷል። (2 ዜና 19:4) በእርግጥም ኢዮሳፍጥ “ይሖዋን በሙሉ ልቡ የፈለገ” ንጉሥ ነበር።—2 ዜና 22:9

11 በዛሬው ጊዜ ይሖዋ ታላቅ የማስተማር ዘመቻ እያካሄደ ሲሆን ሁላችንም በዚህ ሥራ መካፈል እንችላለን። በየወሩ ሌሎችን ስለ አምላክ ቃል በማስተማር ይሖዋን ለማገልገል እንዲነሳሱ የመርዳት ግብ አለህ? አንተ በምታደርገው ጥረት ላይ የይሖዋ በረከት ታክሎበት ሰዎችን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ማስጀመር ትችል ይሆናል። እዚህ ግብ ላይ ለመድረስ ወደ ይሖዋ ትጸልያለህ? ከራስህ ጊዜ ላይ የተወሰነውን መሥዋዕት አድርገህም እንኳ ቢሆን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ለመምራት ፈቃደኛ ነህ? ኢዮሳፍጥ፣ ሕዝቡን ወደ እውነተኛው አምልኮ ለመመለስ ወደ ኤፍሬም ክልል እንደሄደ ሁሉ እኛም ከጉባኤ የራቁትን ለመርዳት ጥረት ማድረግ እንችላለን። የጉባኤ ሽማግሌዎች ደግሞ በክልላቸው ውስጥ የሚገኙ የተወገዱ ሰዎችን ለማግኘትና ለመርዳት ጥረት ሊያደርጉ ይችላሉ፤ እነዚህ ሰዎች ቀደም ሲል ይፈጽሙት የነበረውን መጥፎ ድርጊት ትተው ሊሆን ይችላል።

12, 13. (ሀ) ኢዮሳፍጥ የሚያስፈራ ሁኔታ ሲያጋጥመው ምን አደረገ? (ለ) አቅማችን ውስን እንደሆነ በመገንዘብ ረገድ የኢዮሳፍጥን ምሳሌ መከተላችን ምን ጥቅም አለው?

12 እንደ አባቱ እንደ አሳ ሁሉ ኢዮሳፍጥም አስፈሪ የሆነ የጠላት ሠራዊት በመጣበት ጊዜም እንኳ ሙሉ በሙሉ ለአምላክ ያደረ መሆኑን አሳይቷል። (2 ዜና መዋዕል 20:2-4ን አንብብ።) ኢዮሳፍጥ ፈርቶ ስለነበር “[ይሖዋን] ለመፈለግ ቆርጦ ተነሳ።” እሱም ሆነ ሕዝቡ “ይህን ታላቅ ሠራዊት ለመቋቋም የሚያስችል ኃይል” እንደሌላቸው በመግለጽ ትሕትና የተሞላበት ጸሎት አቅርቧል፤ አክሎም “ምን ማድረግ እንዳለብንም አናውቅም” ሲል ተናግሯል። “ዓይኖቻችን ወደ አንተ ይመለከታሉ” በማለት በይሖዋ ሙሉ በሙሉ እንደሚታመን ገልጿል።—2 ዜና 20:12

13 ልክ እንደ ኢዮሳፍጥ ሁሉ እኛም አንዳንድ ጊዜ፣ ችግር ሲያጋጥመን ምን ማድረግ እንዳለብን ግራ እንጋባ ምናልባትም በፍርሃት እንዋጥ ይሆናል። (2 ቆሮ. 4:8, 9) በዚህ ጊዜ፣ ኢዮሳፍጥ ምን እንዳደረገ ማስታወሳችን ጠቃሚ ነው፤ እሱም ሆነ የይሁዳ ሰዎች ጠላቶቻቸውን የመቋቋም አቅም እንደሌላቸው በሕዝቡ ፊት ባቀረበው ጸሎት ላይ ገልጿል። (2 ዜና 20:5) የቤተሰብ ራሶች ችግር በሚያጋጥማቸው ጊዜ ይሖዋ አስፈላጊውን መመሪያና ሁኔታውን ለመቋቋም የሚያስችል ብርታት እንዲሰጣቸው በመለመን የኢዮሳፍጥን ምሳሌ መከተል ይችላሉ። በቤተሰብህ ፊት እንዲህ ዓይነት ልመና ማቅረብ ሊያሳፍርህ አይገባም። የቤተሰብህ አባላት እንዲህ ያለ ጸሎት ስታቀርብ መስማታቸው በይሖዋ እንደምትታመን እንዲገነዘቡ ያደርጋቸዋል። አምላክ ኢዮሳፍጥን እንደረዳው ሁሉ አንተንም ይረዳሃል።

ሕዝቅያስ ትክክል የሆነውን ነገር አድርጓል

14, 15. ሕዝቅያስ በአምላክ ሙሉ በሙሉ እንደሚታመን ያሳየው እንዴት ነው?

14 “ከይሖዋ ጋር [እንደተጣበቀ]” የተነገረለት ሌላው ንጉሥ ሕዝቅያስ ነው፤ ከኢዮሳፍጥ በተለየ መልኩ ሕዝቅያስ፣ ጣዖት አምላኪ የነበረው አባቱ የሚያሳድረውን መጥፎ ተጽዕኖ መቋቋም ነበረበት። ሕዝቅያስ ‘ከፍ ያሉትን የማምለኪያ ቦታዎች አስወግዷል፤ የማምለኪያ ዓምዶቹን አድቅቋል እንዲሁም የማምለኪያ ግንዱን ቆራርጧል።’ በተጨማሪም ሕዝቡ በዚያ ዘመን ለጣዖት አምልኮ ያዋሉትን “ሙሴ ሠርቶት የነበረውን የመዳብ እባብ [አድቅቋል]።” ሕዝቅያስ “ይሖዋ ለሙሴ የሰጠውን ትእዛዝ ጠብቆ” እንደኖረ ስለተገለጸ ሙሉ በሙሉ ለይሖዋ ያደረ ንጉሥ እንደነበር መረዳት ይቻላል።—2 ነገ. 18:1-6

15 በዘመኑ የዓለም ኃያል የነበረው የአሦር መንግሥት ይሁዳን በወረረበትና ኢየሩሳሌምን ለማጥፋት እየዛተ በነበረበት ወቅትም እንኳ ሕዝቅያስ በሙሉ ልቡ በይሖዋ እንደሚታመን አሳይቷል። የአሦር ንጉሥ ሰናክሬም፣ በይሖዋ ላይ የተሳለቀ ሲሆን ሕዝቅያስን በማስፈራራት እሱም ሆነ ሕዝቡ እጃቸውን እንዲሰጡ ለማድረግ ሞክሮ ነበር። ሕዝቅያስ ግን ለይሖዋ ባቀረበው ጸሎት ላይ በእሱ የማዳን ኃይል ሙሉ በሙሉ እንደሚታመን ገልጿል። (ኢሳይያስ 37:15-20ን አንብብ።) አምላክም መልአኩን ልኮ 185,000 አሦራውያንን እንዲገድል በማድረግ ለሕዝቅያስ ጸሎት መልስ ሰጥቷል።—ኢሳ. 37:36, 37

16, 17. አምላክን ከማገልገል ጋር በተያያዘ የሕዝቅያስን ምሳሌ መከተል የምትችለው እንዴት ነው?

16 በአንድ ወቅት ሕዝቅያስ በጠና ታሞ ሞት አፋፍ ላይ ደርሶ ነበር። በዚህ ጊዜ ወደ ይሖዋ አጥብቆ በመጸለይ በእሱ ፊት እንዴት እንደተመላለሰ እንዲያስታውስ ለመነው። (2 ነገሥት 20:1-3ን አንብብ።) ይሖዋም ጸሎቱን በመስማት ከሕመሙ ፈወሰው። ቅዱሳን መጻሕፍት እንደሚጠቁሙት በዚህ ዘመን አምላክ በተአምራዊ መንገድ ይፈውሰናል ወይም ዕድሜያችንን ያራዝምልናል ብለን መጠበቅ አንችልም። ያም ቢሆን እንደ ሕዝቅያስ “እባክህ ይሖዋ ሆይ፣ በታማኝነትና በሙሉ ልብ በፊትህ እንዴት እንደተመላለስኩ . . . እንድታስታውስ አጥብቄ እለምንሃለሁ” ብለን መጸለይ እንችላለን። አንተስ በአልጋ ላይ ተኝተህ ሳለ ይሖዋ ሊደግፍህ እንደሚችልና እንደሚንከባከብህ ትተማመናለህ?—መዝ. 41:3

17 ሕዝቅያስ በተወው ምሳሌ ላይ ስናሰላስል፣ ከይሖዋ ጋር ባለን ዝምድና ላይ ተጽዕኖ እያሳደሩ ወይም ለእውነተኛው አምልኮ ሙሉ ትኩረት እንዳንሰጥ እንቅፋት እየሆኑብን ያሉ ነገሮች እንዳሉ ይሰማን ይሆናል። ለምሳሌ በዛሬው ጊዜ ብዙዎች፣ ታዋቂ ሰዎችን እንደ ጣዖት አድርገው ይመለከቷቸዋል፤ በማኅበራዊ ድረ ገጾች አማካኝነት የእነዚህን ሰዎች ሕይወት ለመከታተል ከፍተኛ ጥረት ያደርጋሉ። እርግጥ ነው፣ አንዳንድ ክርስቲያኖች ከቤተሰባቸው አባላት ወይም ከጓደኞቻቸው ጋር ለመገናኘት በማኅበራዊ ድረ ገጾች ይጠቀሙ ይሆናል። ይሁንና በዓለም ላይ ብዙዎች በማኅበራዊ ድረ ገጾች ከልክ በላይ ሲጠቀሙ ይታያሉ፤ በእነዚህ ድረ ገጾች አማካኝነት የማያውቋቸውን ሰዎች ሕይወት እንኳ ይከታተላሉ። የታዋቂ ሰዎችን ፎቶግራፎች በማየት ወይም ስለ እነሱ በማንበብ ብዙ ጊዜ ያጠፋሉ። እንዲህ ዓይነቱ ልማድ እርባና በሌላቸው ነገሮች እንድንጠመድ ሊያደርገን ይችላል። ሌላው ቀርቶ አንዳንድ ክርስቲያኖች፣ ማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ ያስቀመጧቸውን ፎቶግራፎች ብዙዎች ስለወደዱላቸው (ላይክ ስላደረጉላቸው) ይኩራሩ ይሆናል፤ ይባስ ብሎም በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ ሰዎች እነሱን “መከተል” በማቆማቸው ቅር የሚሰኙም አሉ። ሐዋርያው ጳውሎስ፣ አቂላ ወይም ጵርስቅላ ቢሆኑ በየዕለቱ ፎቶግራፋቸውን ማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ በማውጣት ወይም ክርስቲያን ያልሆኑ ሰዎችን ሕይወት በመከታተል ጊዜያቸውን የሚያጠፉ ይመስልሃል? መጽሐፍ ቅዱስ “ጳውሎስ ቃሉን በመስበኩ ሥራ በእጅጉ [እንደተጠመደ]” ይናገራል። ጵርስቅላና አቂላም ጊዜያቸውን የሚያሳልፉት ለሰዎች “የአምላክን መንገድ ይበልጥ በትክክል [በማብራራት]” ነበር። (ሥራ 18:4, 5, 26) እኛም ራሳችንን እንደሚከተለው ብለን መጠየቃችን ጠቃሚ ነው፦ ‘ሰዎችን እንደ ጣዖት የመመልከት ዝንባሌ እንዳላዳብር ወይም ያን ያህል ጥቅም የሌላቸው ነገሮችን በማከናወን ውድ የሆነውን ጊዜዬን እንዳላጠፋ እጠነቀቃለሁ?’—ኤፌሶን 5:15, 16ን አንብብ።

ኢዮስያስ የይሖዋን ትእዛዛት ጠብቋል

18, 19. ኢዮስያስን መምሰል የምትፈልገው በየትኞቹ መንገዶች ነው?

18 የሕዝቅያስ ልጅ የሆነው የምናሴ የልጅ ልጅ፣ ማለትም ንጉሥ ኢዮስያስ የይሖዋን ትእዛዛት “በሙሉ ልቡ” ጠብቋል። (2 ዜና 34:31) ኢዮስያስ ገና በአሥራዎቹ ዕድሜ እያለ “የዳዊትን አምላክ መፈለግ ጀመረ።” ዕድሜው 20 ዓመት ሲሆን ደግሞ የይሁዳን ምድር ከጣዖት አምልኮ ለማጽዳት ተነሳ። (2 ዜና መዋዕል 34:1-3ን አንብብ።) ኢዮስያስ ከብዙዎቹ የይሁዳ ነገሥታት ይበልጥ፣ አምላክን የሚያስደስተውን ነገር በቅንዓት አከናውኗል። በአንድ ወቅት ኢዮስያስ የሙሴ ሕግ መጽሐፍ ተገኝቶ ሲነበብለት፣ የአምላክን ፈቃድ ይበልጥ በተሟላ መንገድ ማድረግ እንደሚያስፈልገው ተገነዘበ። ሌሎችም ይሖዋን እንዲያገለግሉ አበረታታ። በመሆኑም ሕዝቡ በኢዮስያስ የሕይወት ዘመን ሁሉ “የአባቶቻቸውን አምላክ ይሖዋን ከመከተል ፈቀቅ አላሉም።”—2 ዜና 34:27, 33

19 እንደ ኢዮስያስ ሁሉ በዛሬው ጊዜ ያሉ ልጆችም ከትንሽነታቸው አንስቶ ይሖዋን መፈለግ አለባቸው። ንጉሥ ምናሴ ንስሐ ከገባ በኋላ ኢዮስያስን ስለ አምላክ ምሕረት አስተምሮት ሊሆን ይችላል። ልጆች የሆናችሁ፣ በቤተሰባችሁና በጉባኤያችሁ ውስጥ ካሉ ታማኝ የሆኑ ትላልቅ ወንድሞችና እህቶች ጋር ብትቀራረቡ ይሖዋ ስላደረገላቸው በርካታ መልካም ነገሮች ሊነግሯችሁ ይችላሉ። በተጨማሪም ኢዮስያስ ቅዱሳን መጻሕፍት ምን እንደሚሉ ማወቁ ልቡ እንዲነካና እርምጃ እንዲወስድ እንዳነሳሳው አስታውሱ። እናንተም የአምላክን ቃል ማንበባችሁ ደስታችሁ እንዲጨምር፣ ከአምላክ ጋር ያላችሁ ወዳጅነት እንዲጠናከር እንዲሁም ሌሎች አምላክን እንዲፈልጉ ለመርዳት እንድትነሳሱ ሊያደርግ ይችላል። (2 ዜና መዋዕል 34:18, 19ን አንብብ።) ከዚህም ሌላ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናታችሁ ለአምላክ በምታቀርቡት አገልግሎት ረገድ ማሻሻያ ማድረግ የምትችሉባቸውን መንገዶች እንድታስተውሉ ይረዳችኋል። ማሻሻያ ማድረግ እንደሚያስፈልጋችሁ ከተሰማችሁ ልክ እንደ ኢዮስያስ ለውጥ ለማድረግ የተቻላችሁን ጥረት አድርጉ።

ይሖዋን በሙሉ ልብ አገልግሉ!

20, 21. (ሀ) በዚህ ርዕስ ላይ የተመለከትናቸው አራት ነገሥታት ምን የሚያመሳስላቸው ነገር አለ? (ለ) በሚቀጥለው ርዕስ ላይ ምን እንመለከታለን?

20 ይሖዋን በሙሉ ልባቸው ያገለገሉትን አራት የይሁዳ ነገሥታት ታሪክ በመመርመራችን እንደተጠቀምክ ይሰማሃል? እነዚህ ነገሥታት የአምላክን ፈቃድ በቅንዓት እንዲሁም በሙሉ ልባቸው አከናውነዋል። በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ይሖዋን ለማምለክ ጥረት አድርገዋል። ኃያል ጠላቶች ቢነሱባቸውም እንኳ ይህን ከማድረግ ወደኋላ አላሉም። ከሁሉ በላይ ደግሞ ይሖዋን እንዲያገለግሉ ያነሳሳቸው ለእሱ ያላቸው ፍቅር ነው።

21 በቀጣዩ ርዕስ ላይ እንደምንመለከተው አራቱም ነገሥታት ስህተት የሠሩባቸው ጊዜያት አሉ። ይሁንና ልብን የሚመረምረው አምላክ በሙሉ ልባቸው እንዳገለገሉት ገልጿል። እኛም ብንሆን ፍጽምና የጎደለን በመሆናችን ስህተት እንሠራለን። ሆኖም ይሖዋ ልባችንን ሲመረምር በሙሉ ልባችን እንደምናገለግለው ይሰማው ይሆን? የሚቀጥለው ርዕስ እነዚህ አራት ነገሥታት ከፈጸሟቸው ስህተቶች ምን ትምህርት ልናገኝ እንደምንችል ያብራራል።